በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

‘ማርና ወተት የምታፈሰው ምድር’

‘ማርና ወተት የምታፈሰው ምድር’

‘ማርና ወተት የምታፈሰው ምድር’

ይሖዋ አምላክ እስራኤላውያንን ከግብፅ ባርነት ነፃ ሲያወጣቸው ‘ማርና ወተት ወደምታፈሰው ሰፊና ለም ምድር’ እንደሚያስገባቸው ቃል ገብቶላቸው ነበር።—ዘፀአት 3:8

እስራኤላውያን ተስፋይቱ ምድር ከገቡ በኋላ ላሞችን፣ በጎችንና ፍየሎችን ማርባት በመጀመራቸው ከፍተኛ የወተት ምርት ያገኙ ነበር። ይሁንና ማርን በተመለከተስ ምን ማለት ይቻላል? አንዳንዶች ማር የሚለው ቃል ከቴምር፣ ከበለስ ወይም ከወይን ይዘጋጅ የነበረውን ጣፋጭ ፈሳሽ እንደሚያመለክት ይሰማቸዋል። ከንብ ስለሚገኘው ማር የሚናገሩ አብዛኞቹ የመጽሐፍ ቅዱስ ጥቅሶች ማሩ ተመርቶ ሳይሆን ከጫካ የተገኘ መሆኑን የሚጠቁሙ ናቸው። (መሳፍንት 14:8, 9፤ 1 ሳሙኤል 14:27፤ ማቴዎስ 3:1, 4) በእርግጥ ምድሪቱ ልክ እንደ ወተት ሁሉ ማርም ‘የምታፈስ’ ነበረች?

በቅርቡ በዘመናዊቷ እስራኤል በመሬት ቁፋሮ የተገኘው ነገር ስለሁኔታው ግልጽ የሆነ መረጃ አስገኝቷል። የሂብሩ ዩኒቨርሲቲ ግኝቱን አስመልክቶ በሰጠው ጋዜጣዊ መግለጫ ላይ እንደሚከተለው ብሏል፦ “ፕሮፌሰር (አሚሃይ) ማዛር በመካከለኛው ምሥራቅ እስካሁን ድረስ በአርኪኦሎጂ ቁፋሮ ከተገኙት የንብ ቀፎዎች ይህ ጥንታዊው እንደሆነ ገልጸዋል። ይህ ቀፎ ከ10ኛው እስከ 9ኛው መቶ ዘመን ዓ.ዓ. መጀመሪያ አካባቢ ድረስ አገልግሎት ሲሠጥ የነበረ ነው።”

የአርኪኦሎጂ ባለሙያዎቹ በሦስት ደርብ በረድፍ የተቀመጡ ከ30 የሚበልጡ ቀፎዎችን ያገኙ ሲሆን ቦታው መቶ ገደማ የሚሆኑ ቀፎዎችን ሊይዝ እንደሚችል ገምተዋል። በቀፎዎቹ ላይ በተደረገው ጥናት የንቦች አካልና የሰም ሞለኪዩል ተገኝቷል። ምሑራን እንደገመቱት “ከእነዚህ የንብ ቀፎዎች በየዓመቱ እስከ 500 ኪሎ ግራም የሚመዝን ማር ይመረት ነበር።”

በጥንት ጊዜ ማር ለምግብነት ብቻ ሳይሆን ሰሙ በብረትና በቆዳ ኢንዱስትሪ ውስጥ በጥሬ ዕቃነት ያገለግል ነበር። በተጨማሪም ሰም ለመጻፊያነት የሚያገለግል የእንጨት ጽላት ለማዘጋጀት ይውል ነበር፤ እንዲህ ያለው ጽላት የሚዘጋጀው በእንጨት ፍሬም ላይ ሰም በማፍሰስ ሲሆን ሰሙ በድጋሚ ቀልጦ አገልግሎት ላይ ሊውል ይችላል። ታዲያ አርኪኦሎጂስቶቹ እነዚህን ቀፎዎች ማግኘታቸው ምን መደምደሚያ ላይ እንዲደርሱ አድርጓቸዋል?

ጋዜጣዊ መግለጫው በመቀጠል እንዲህ ሲል አትቷል፦ “መጽሐፍ ቅዱስ በዚያን ዘመን በእስራኤል የንብ ማነብ ሥራ ይካሄድ እንደነበር የሚናገረው ነገር ባይኖርም በቴል ረሆቭ የንብ ቀፎዎች መገኘታቸው የመጀመሪያው [የሰለሞን] ቤተ መቅደስ በተገነባበት ዘመን ንብ ማነብና ማሩን ከሰሙ ማጣራት ከፍተኛ ደረጃ ላይ የደረሰ ኢንዱስትሪ እንደነበር ይጠቁማል። በመሆኑም መጽሐፍ ቅዱስ ‘ማር’ በማለት የገለጸው የንብ ማር ሊሆን ይችላል።”

[በገጽ 15 ላይ የሚገኝ የሥዕል ምንጭ]

Institute of Archaeology/Hebrew University © Tel Rehov Excavations