በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ለቤተሰብ | ትዳር

የአመለካከት ልዩነቶችን ማስታረቅ

የአመለካከት ልዩነቶችን ማስታረቅ

ተፈታታኙ ነገር

አንተ ስፖርት ትወድ ይሆናል፤ ባለቤትህ ደግሞ ማንበብ ትመርጣለች። አንተ ጠንቃቃና የተደራጀህ ስትሆን እሷ ግን እንዲህ አይደለችም። አንተ አብዛኛውን ጊዜ ከሰዎች ጋር መሆን ትፈልግ ይሆናል፤ እሷ ደግሞ ብቻዋን መሆን ትመርጣለች።

‘ፍጹም የተለያየን ሰዎች ነን። በምንጠናናበት ወቅት እንዴት ይህን ሳላስተውል ቀረሁ?’ ብለህ ታስባለህ።

እርግጥ ያን ጊዜም ቢሆን በተወሰነ ደረጃ ሳታስተውለው አልቀረህም። ይሁንና በዚያ ወቅት እነዚህ ልዩነቶች በቀላሉ ታልፋቸው የነበሩ ነገሮች ሊሆኑ ይችላሉ፤ አሁንም ይህን ማድረግህ አስፈላጊ ነው። ይህ ርዕስ በዚህ ረገድ ይረዳሃል። በመጀመሪያ ግን ስለ አመለካከት ልዩነት አንዳንድ እውነታዎችን እንመልከት።

ማወቅ የሚኖርባችሁ ነገር

አንዳንድ ልዩነቶች ትልቅ ለውጥ የሚያመጡ ናቸው። አንድ ወንድና ሴት የሚጠናኑበት ዋነኛ ዓላማ እርስ በርስ የሚጣጣሙ መሆናቸውን ለማወቅ ነው። በመሆኑም በሚጠናኑበት ወቅት፣ ትልቅ ለውጥ የሚያመጡ ልዩነቶች እንዳሏቸው ከተገነዘቡ አንድነት የሌለበት ትዳር ውስጥ በጭፍን ከመግባት ይልቅ ግንኙነታቸውን ለማቋረጥ መወሰናቸው ጥበብ ነው። በየትኛውም ትዳር ውስጥ ስለሚኖሩት ቀላል ልዩነቶችስ ምን ማለት ይቻላል?

ፍጹም አንድ ዓይነት የሆኑ ሰዎች የሉም። በመሆኑም የትዳር ጓደኛሞች ቀጥሎ ከተዘረዘሩት ነጥቦች ቢያንስ በአንዱ ቢለያዩ አያስገርምም፦

ፍላጎት፦ አና * የተባለች ሴት እንዲህ ብላለች፦ “ከቤት ውጭ መዝናናት ምንም አያስደስተኝም፤ ባለቤቴ ግን ከልጅነቱ ጀምሮ በበረዶ የተሸፈኑ ተራራዎችን መውጣት እንዲሁም ለቀናት በጫካ ውስጥ መጓዝ ያስደስተዋል።”

ልማድ፦ “ባለቤቴ ማምሸት ትችላለች፤ በጣም አምሽታም እንኳ 11 ሰዓት ላይ ንቁ ሆና ትነሳለች። እኔ ግን ሰባት ወይም ስምንት ሰዓት ያህል ካልተኛሁ ያነጫንጨኛል” በማለት ብራያን የተባለ ሰው ተናግሯል።

ባሕርይ፦ አንተ በባሕርይህ ቁጥብ ስትሆን ባለቤትህ ግን ስሜቷን አውጥታ መግለጽ አይከብዳት ይሆናል። ዴቪድ እንዲህ ብሏል፦ “ከልጅነቴ ጀምሮ የግል ችግሬን ለሌላ ሰው መናገር ይከብደኛል፤ ባለቤቴ ደግሞ ያደገችው ሁሉ ነገር በግልጽ በሚወራበት ቤተሰብ ውስጥ ነው።”

ልዩነት መኖሩ ጠቃሚ ሊሆን ይችላል። ሄለና የተባለች ሴት “እኔ አንድን ነገር የማደርግበት መንገድ ጥሩ ሊሆን ይችላል፤ ይህ ማለት ግን ያንን ነገር ማከናወን የሚቻልበት ሌላ መንገድ የለም ማለት አይደለም” ብላለች።

ምን ማድረግ ትችላላችሁ?

የትዳር ጓደኛችሁን ደግፉ። አዳም የተባለ አንድ ሰው ስለ ትዳር ጓደኛው ሲናገር እንዲህ ብሏል፦ “ኬረን ስፖርት አትወድም። ያም ቢሆን ጨዋታ ልመለከት ስሄድ ብዙ ጊዜ አብራኝ ትመጣለች፤ እንዲያውም ከእኔ ጋር ደስታዋን ትገልጻለች። በሌላ በኩል ደግሞ ኬረን የሥነ ጥበብ ሙዚየሞችን መጎብኘት ትወዳለች፤ እኔም ከእሷ ጋር ሄጄ የፈለገችውን ያህል ጊዜ አብሬያት አሳልፋለሁ። እሷ ሥነ ጥበብ ስለምትወድ ለሥነ ጥበብ አድናቆት ለማዳበር ጥረት አደርጋለሁ።”—የመጽሐፍ ቅዱስ መመሪያ፦ 1 ቆሮንቶስ 10:24

የአመለካከት አድማሳችሁን አስፉ። የትዳር ጓደኛህ አመለካከት ከአንተ ስለተለየ ብቻ የተሳሳተ ነው ማለት አይደለም። አሌክስ ይህን የተገነዘበው ከጊዜ በኋላ ነው። እንዲህ ብሏል፦ “አንድን ነገር ውጤታማ በሆነ መንገድ ለማከናወን እኔ ካሰብኩት ውጪ ሌላ አማራጭ እንዳለ አይሰማኝም ነበር። የትዳር ሕይወት ግን አንድን ነገር ውጤታማ በሆነ መንገድ ለመሥራት በርካታ አማራጮች እንዳሉ አስገንዝቦኛል፤ እያንዳንዱ አማራጭ ደግሞ የራሱ የሆነ ጥቅም አለው።”—የመጽሐፍ ቅዱስ መመሪያ፦ 1 ጴጥሮስ 5:5

ምክንያታዊ ሁኑ። መጣጣም ሲባል አንድ ዓይነት መሆን ማለት አይደለም። በመሆኑም ከባለቤትህ ጋር በአንዳንድ ጉዳዮች ስለተለያያችሁ ብቻ የትዳር ጓደኛ ምርጫህ ስህተት እንደሆነ ሊሰማህ አይገባም። ዘ ኬዝ አጌንስት ዲቮርስ የተሰኘው መጽሐፍ እንዲህ ይላል፦ “ብዙ ሰዎች ‘ፍቅር አሳውሮኝ ነው’ የሚል ሰበብ ያቀርባሉ። ሆኖም . . . በደስታ ያሳለፋችሁት እያንዳንዱ ቀን፣ ምንም ዓይነት ልዩነት ቢኖራችሁ ልትዋደዱ እንደምትችሉ ያሳያል።” “አንዱ በሌላው ላይ ቅር የተሰኘበት ነገር ቢኖረው እንኳ እርስ በርስ መቻቻላችሁን . . . ቀጥሉ።”—ቆላስይስ 3:13

እንዲህ ለማድረግ ሞክሩ፦ ከትዳር ጓደኛችሁ ጋር በተያያዘ የምትወዱትንና የሚያስደስታችሁን እንዲሁም እርስ በርስ የምትመሳሰሉበትን ነገር ጻፉ። ከዚያም የማትመሳሰሉባቸውን ነገሮች ጻፉ። እንዲህ ስታደርጉ የአመለካከት ልዩነቶቻችሁ እምብዛም ለውጥ የማያመጡ እንደሆኑ ትገነዘቡ ይሆናል። በተጨማሪም ያዘጋጃችሁት ዝርዝር የትዳር ጓደኛችሁን መደገፍ ወይም እርስ በርስ መቻቻል የምትችሉባቸውን አቅጣጫዎች ለማወቅ ያስችላችኋል። ኬኔት “ባለቤቴ እኔ የምፈልገውን ነገር ስታደርግልኝ ደስ ይለኛል፤ እኔም እንደዛ ሳደርግላት ደስ እንደሚላት አውቃለሁ” ብሏል። አክሎም “መሥዋዕት መክፈል ቢጠይቅብኝም እንኳ እሷ ስትደሰት ማየት ያስደስተኛል” በማለት ተናግሯል።—የመጽሐፍ ቅዱስ መመሪያ፦ ፊልጵስዩስ 4:5

^ አን.10 በዚህ ርዕስ ውስጥ የተጠቀሱት አንዳንዶቹ ስሞች ተቀይረዋል።