በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

አምላክ እንደሚያስብልህ ማወቅህ የሚጠቅምህ እንዴት ነው?

አምላክ እንደሚያስብልህ ማወቅህ የሚጠቅምህ እንዴት ነው?

አምላክ ሰውነታችንን የፈጠረው ራሱን በራሱ የመጠገን አስደናቂ ችሎታ እንዲኖረው አድርጎ ነው። አንድ ጤናማ ሰው የሆነ ነገር ሲቆርጠው፣ ሲልጠው ወይም ሲወጋው ሰውነቱ “ከባድም ሆነ ቀላል ቁስሎችን ለመጠገን የሚያስችሉ ውስብስብና የተቀነባበሩ ሂደቶች መከናወን እንዲጀምሩ ያደርጋል።” (ጆን ሆፕኪንስ ሜዲስን) በዚህ መንገድ ሰውነቱ ወዲያውኑ ደሙን ለማስቆም፣ ቁስሉን ለመጠገንና የተጎዳውን ሕብረ ሕዋስ ለማጠናከር ሥራውን ይጀምራል።

እስቲ አስበው፦ ሰውነታችንን ቁስሎችን የመጠገን ችሎታ እንዲኖረው አድርጎ የፈጠረው አምላክ ከስሜታዊ ጉዳቶችም እንድናገግም እንደሚረዳን በገባው ቃል ላይ እምነት መጣል ምክንያታዊ አይሆንም? መዝሙራዊው “የተሰበረ ልብ ያላቸውን ይጠግናል፤ ቁስላቸውን ይፈውሳል” በማለት ጽፏል። (መዝሙር 147:3) ይሁን እንጂ ከዚህ በፊት ያጋጠመህ ወይም አሁን እየደረሰብህ ያለ ነገር ባስከተለብህ ስሜታዊ ጉዳት የተነሳ እየተሠቃየህ ከሆነ ይሖዋ አሁንም ሆነ ወደፊት ቁስልህን እንደሚፈውስልህ እርግጠኛ መሆን የምትችለው እንዴት ነው?

መጽሐፍ ቅዱስ አምላክ እንደሚያስብልን የሚያሳይ ምን ማስረጃ ይዟል?

አምላክ እንዲህ ሲል ቃል ገብቶልናል፦ “እኔ ከአንተ ጋር ነኝና አትፍራ። እኔ አምላክህ ነኝና አትጨነቅ። አበረታሃለሁ፤ አዎ እረዳሃለሁ።” (ኢሳይያስ 41:10) ይሖዋ እንደሚያስብለት የሚያውቅ ሰው የአእምሮ ሰላምና የተለያዩ መከራዎችን ለመቋቋም የሚያስችል ብርታት ይኖረዋል። ሐዋርያው ጳውሎስ ይህን ውስጣዊ መረጋጋት “ከመረዳት ችሎታ ሁሉ በላይ የሆነው የአምላክ ሰላም” በማለት ጠርቶታል። አክሎም “ኃይልን በሚሰጠኝ በእሱ አማካኝነት ለሁሉም ነገር የሚሆን ብርታት አለኝ” ብሏል።—ፊልጵስዩስ 4:4-7, 9, 13

መጽሐፍ ቅዱስ ይሖዋ ወደፊት ለሰው ዘር በሰጠው ተስፋ ላይ እምነት ለመገንባት ይረዳናል። ለምሳሌ ያህል፣ ራእይ 21:4, 5 ይሖዋ ወደፊት ምን እንደሚያደርግና እሱ የሰጠው ተስፋ መፈጸሙ እንደማይቀር መተማመን የምንችለው ለምን እንደሆነ ይነግረናል፦

  • “እንባን ሁሉ [ከዓይናችን] ያብሳል።” ይሖዋ ሌሎች እንደ ቀላል ነገር የሚያዩትን ጨምሮ የሚደርስብንን ማንኛውንም መከራና ሥቃይ ያስወግዳል።

  • ‘በዙፋኑ ላይ’ በሰማያዊ ክብሩ የተቀመጠው ሁሉን ቻይ የሆነው የፍጥረታት ሁሉ ንጉሥ መከራን ለማስቀረትና የሚያስፈልገንን እርዳታ ለመስጠት ኃይሉንና ሥልጣኑን ይጠቀምበታል።

  • ይሖዋ፣ እሱ የሰጣቸው ተስፋዎች “አስተማማኝና እውነት” እንደሆኑ ማረጋገጫ ሰጥቶናል። እውነተኛ አምላክ እንደመሆኑ መጠን ያተረፈው ስም እሱ የገባው ቃል መፈጸሙ እንደማይቀር የሚያረጋግጥ ዋስትና ይሆነናል።

“‘እሱም እንባን ሁሉ ከዓይናቸው ያብሳል፤ ከእንግዲህ ወዲህ ሞት አይኖርም፤ ሐዘንም ሆነ ጩኸት እንዲሁም ሥቃይ ከእንግዲህ ወዲህ አይኖርም። ቀድሞ የነበሩት ነገሮች አልፈዋል።’ በዙፋኑም ላይ የተቀመጠው ‘እነሆ፣ ሁሉንም ነገር አዲስ አደርጋለሁ’ አለ። ደግሞም ‘እነዚህ ቃላት አስተማማኝና እውነት ስለሆኑ ጻፍ’ አለኝ።”—ራእይ 21:4, 5

ግዑዙ ጽንፈ ዓለምም ሆነ መጽሐፍ ቅዱስ በሰማይ ያለውን አባታችንን ማንነትና ባሕርያት ይገልጹልናል። ፍጥረት አምላክን የቅርብ ወዳጃችን ያህል እንድናውቀው በተዘዋዋሪ መንገድ ግብዣ የሚያቀርብልን ሲሆን መጽሐፍ ቅዱስ ደግሞ “ወደ አምላክ ቅረቡ፤ እሱም ወደ እናንተ ይቀርባል” በማለት ቀጥተኛ ግብዣ ያቀርብልናል። (ያዕቆብ 4:8) የሐዋርያት ሥራ 17:27 “እሱ ከእያንዳንዳችን የራቀ . . . አይደለም” በማለት ይናገራል።

ጊዜ መድበህ አምላክን ለማወቅ ጥረት ባደረግህ መጠን ‘እሱ ስለ አንተ እንደሚያስብ’ ይበልጥ እርግጠኛ እየሆንክ ትሄዳለህ። (1 ጴጥሮስ 5:7) በይሖዋ ላይ እንዲህ ያለ እምነት መጣል ምን ጥቅሞች አሉት?

በጃፓን የሚኖረውን የቶሩን ሁኔታ ተመልከት። እናቱ በክርስትና እምነት ውስጥ ብታሳድገውም እሱ ግን በዓመፀኝነቱ የሚታወቀውን ያኩዛ የሚባለውን የጃፓን ማፊያ ቡድን ተቀላቀለ። እንዲህ ሲል ተናግሯል፦ “አምላክ እንደሚጠላኝና የምቀርባቸው ሰዎች በተለይም በጣም የምወዳቸው ሰዎች እንዲሞቱ የሚያደርገው እኔን ለመቅጣት እንደሆነ ይሰማኝ ነበር።” ቶሩ ዓመፀኛ ከሆኑ ሰዎች ጋር መግጠሙና መጥፎ አስተሳሰብ መያዙ “ጨካኝና ምንም ርኅራኄ የሌለው ሰው” እንዲሆን እንዳደረገው ሳይሸሽግ ተናግሯል። በወቅቱ ይመኝ ስለነበረው ነገር ሲናገር “ከእኔ የበለጠ ታዋቂ የሆነ ሰው ገድዬ ለራሴ ስም ካተረፍኩ በኋላ ገና ወጣት ሳለሁ መሞት እፈልግ ነበር” ብሏል።

ሆኖም ቶሩና ባለቤቱ ሐና መጽሐፍ ቅዱስን ማጥናት ከጀመሩ በኋላ ቶሩ በአኗኗሩና በአመለካከቱ ላይ አስገራሚ ለውጥ ማድረግ ጀመረ። ሐና “ባለቤቴ የሚያደርገውን ለውጥ በግልጽ ማየት ችያለሁ” ብላለች። በአሁኑ ጊዜ ቶሩ እንዲህ በማለት በእርግጠኝነት ይናገራል፦ “በእርግጥም ለእያንዳንዳችን ከልብ የሚያስብ አምላክ አለ። እሱ ማንም እንዲሞት የማይፈልግ ሲሆን ከስህተታቸው ከልብ ንስሐ የሚገቡ ሰዎችን ይቅር ለማለት ዝግጁ ነው። ከእሱ በቀር ለማንም የማንናገረውንና ብንናገርም ማንም የማይረዳልንን ነገር ስንነግረው ይሰማናል። በቅርቡ ይሖዋ ማንኛውንም ችግር፣ ሥቃይና መከራ ያስወግዳል። አሁንም እንኳ ፈጽሞ ባልጠበቅናቸው መንገዶች እርዳታ ያደርግልናል። መንፈሳችን ሲደቆስ ፍቅሩን የሚያሳየን ከመሆኑም ሌላ ይደግፈናል።”—መዝሙር 136:23

የቶሩ ተሞክሮ እንደሚያሳየው አምላክ ሐዘን የሚያስከትሉ ነገሮችን ሁሉ ማስወገድ እንደሚችልና በቅርቡም እንዲህ እንደሚያደርግ ማወቃችን ስለ ወደፊቱ ጊዜ የተረጋገጠ ተስፋ እንዲኖረን ብቻ ሳይሆን በአሁኑ ጊዜም የተሻለ ሕይወት እንድንኖር ያስችለናል። አዎ፣ በመከራ በተሞላው በዚህ ዓለም ውስጥ እንኳ የአምላክን ፍቅራዊ እንክብካቤ ማግኘት እንችላለን።