በቀጥታ ወደ ዋናው ጉዳይ ግባ

በቀጥታ ወደ ርዕስ ማውጫው ሂድ

ልክ እንደ ኮምፓስ ሁሉ ጥሩ የሥነ ምግባር መሥፈርቶችም ልጃችሁ ትክክለኛውን አቅጣጫ መለየት እንዲችል ይረዱታል

ለወላጆች

7፦ በሥነ ምግባር መሥፈርቶች መመራት

7፦ በሥነ ምግባር መሥፈርቶች መመራት

ምን ማለት ነው?

የሥነ ምግባር መሥፈርቶች ሕይወታችንን ለመምራት የምንጠቀምባቸው መሠረታዊ መመሪያዎች ናቸው። ለምሳሌ ያህል፣ በሁሉም ነገር ሐቀኛ ለመሆን ጥረት ታደርጋላችሁ? ከሆነ ልጆቻችሁም እንዲህ ያለውን የሥነ ምግባር መሥፈርት እንዲከተሉ መፈለጋችሁ አይቀርም።

በተጨማሪም ልጆቻችሁ ታታሪ፣ የማያዳሉና ለሌሎች የሚያስቡ እንዲሆኑ ተገቢውን ሥልጠና መስጠታችሁ በጣም አስፈላጊ ነው፤ አንድ ወላጅ ልጆቹ እንዲህ ያሉትን ባሕርያት እንዲያዳብሩ በመርዳት ረገድ ይበልጥ ውጤታማ የሚሆነው ሥልጠናውን ልጆቹ ገና ትንሽ እያሉ ከጀመረ ነው።

የመጽሐፍ ቅዱስ መመሪያ፦ “ልጅን ሊሄድበት በሚገባው መንገድ አሠልጥነው፤ በሚያረጅበት ጊዜም እንኳ ከዚያ ፈቀቅ አይልም።”—ምሳሌ 22:6

አስፈላጊ የሆነው ለምንድን ነው?

ቴክኖሎጂ በተራቀቀበት በዚህ ዘመን የሥነ ምግባር መሥፈርት አስፈላጊ ነው። ካረን የምትባል አንዲት እናት “መጥፎ ተጽዕኖ የሚያሳድሩ ነገሮች በማንኛውም የኤሌክትሮኒክ መሣሪያ ላይ በማንኛውም ጊዜ ሊገኙ ይችላሉ” በማለት ተናግራለች። አክላም “ልጆቻችን አጠገባችን ቁጭ ብለው እንኳ መጥፎ ነገር ሊመለከቱ ይችላሉ!” ብላለች።

የመጽሐፍ ቅዱስ መመሪያ፦ “[ጎልማሳ ሰዎች] ትክክልና ስህተት የሆነውን ነገር መለየት እንዲችሉ የማስተዋል ችሎታቸውን በማሠራት [ያሠለጥናሉ]።”—ዕብራውያን 5:14

ስለ ሌሎች ማሰብ በጣም አስፈላጊ ነው። ይህ “እባክህ” እና “አመሰግናለሁ” እንደሚሉት ያሉ ቀላል የሚመስሉ መግለጫዎችን መጠቀምንና ለሌሎች አሳቢነት ማሳየትን ይጨምራል፤ አጠገባቸው ካሉ ሰዎች ይልቅ ለኤሌክትሮኒክ መሣሪያዎች ትልቅ ግምት የሚሰጡ ሰዎች በሞሉበት በዚህ ዘመን እንዲህ ያለውን ምግባር ማሳየት ያን ያህል የተለመደ አይደለም።

የመጽሐፍ ቅዱስ መመሪያ፦ “ልክ ሰዎች እንዲያደርጉላችሁ እንደምትፈልጉት ሁሉ እናንተም እንዲሁ አድርጉላቸው።”—ሉቃስ 6:31

ምን ማድረግ ትችላላችሁ?

የምትመሩባቸውን የሥነ ምግባር መሥፈርቶች በግልጽ ንገሯቸው። ከጋብቻ በፊት የፆታ ግንኙነት መፈጸም ትክክል እንዳልሆነ በግልጽ የተነገራቸው ወጣቶች ከዚህ ድርጊት የመራቅ አጋጣሚያቸው ሰፊ እንደሚሆን በመስኩ የተደረገ ጥናት ያሳያል።

ጠቃሚ ምክር፦ የሥነ ምግባር መሥፈርቶችን በተመለከተ ከልጆቻችሁ ጋር ውይይት ለመጀመር የሚያስችሏችሁን አጋጣሚዎች ተጠቀሙባቸው። ለምሳሌ ያህል፣ በጥላቻ ምክንያት ስለተፈጸመ ወንጀል የሚገልጽ ዜና ስትሰሙ እንዲህ ማለት ትችላላችሁ፦ “አንዳንድ ሰዎች ሌሎች ሲያበሳጯቸው የሚወስዱት እርምጃ በጣም ዘግናኝ ነው። ሰዎች እንዲህ ዓይነት ወንጀል የሚፈጽሙት ለምን ይመስልሃል?”

“ልጆች የትኛው ትክክል የትኛው ደግሞ ስህተት እንደሆነ ካላወቁ ትክክልና ስህተት የሆነውን መለየት ያዳግታቸዋል።”—ብራንደን

ልጆቻችሁን ስለ ሌሎች እንዲያስቡ አስተምሯቸው። ትናንሽ ልጆችም እንኳ “እባክህ” እና “አመሰግናለሁ” ማለትን እንዲሁም ለሰዎች አክብሮት ማሳየትን ሊማሩ ይችላሉ። ፓረንቲንግ ዊዝአውት ቦርደርስ የተባለው መጽሐፍ እንዲህ ብሏል፦ “ልጆች ስለ ራሳቸው ብቻ ሳይሆን ስለ ቤተሰባቸው፣ በትምህርት ቤት ስለሚያገኟቸው ሰዎች እንዲሁም ስለማኅበረሰቡ ማሰብ እንዳለባቸው ከተገነዘቡ ሌሎች ሰዎችን የሚጠቅሙ የደግነት ሥራዎችን ለማከናወን ይበልጥ ይነሳሳሉ።”

ጠቃሚ ምክር፦ ልጆቻችሁ ሌሎችን የማገልገልን አስፈላጊነት እንዲገነዘቡ የቤት ውስጥ ሥራዎችን እንዲሠሩ አድርጉ።

“ልጆቻችሁ ከእናንተ ጋር እያሉ የቤት ውስጥ ሥራዎችን መሥራት ከለመዱ ራሳቸውን ችለው መኖር ሲጀምሩ አይደናገጡም። ምክንያቱም ኃላፊነቶቻቸውን እንዴት መወጣት እንዳለባቸው ቀደም ብለው ሠልጥነዋል።”—ታራ