ለተሰሎንቄ ሰዎች የተጻፈ የመጀመሪያው ደብዳቤ 2:1-20

  • ጳውሎስ በተሰሎንቄ ያከናወነው አገልግሎት (1-12)

  • የተሰሎንቄ ሰዎች የአምላክን ቃል ተቀበሉ (13-16)

  • ጳውሎስ የተሰሎንቄ ክርስቲያኖችን ለማየት ናፈቀ (17-20)

2  ወንድሞች፣ የእኛ ወደ እናንተ መምጣት ፍሬ ቢስ ሆኖ እንዳልቀረ እናንተ ራሳችሁ እንደምትገነዘቡ ምንም ጥርጥር የለውም።+  እንደምታውቁት በመጀመሪያ በፊልጵስዩስ+ መከራና እንግልት ደርሶብን ነበር፤ ይሁንና ከባድ ተቃውሞ እያለም* የአምላክን ምሥራች ለእናንተ ለመንገር+ በአምላካችን እርዳታ እንደ ምንም ብለን ድፍረት አገኘን።  የምንሰጠው ምክር ከተሳሳተ ሐሳብ ወይም ከመጥፎ ዓላማ የመነጨ ወይም ደግሞ ማታለያ ያዘለ አይደለም፤  ሆኖም ምሥራቹን በአደራ ለመቀበል በአምላክ ዘንድ ብቁ ሆነን የተቆጠርን እንደመሆናችን መጠን የምንናገረው ሰዎችን ለማስደሰት ሳይሆን ልባችንን የሚመረምረውን+ አምላክ ለማስደሰት ብለን ነው።  እንዲያውም የሽንገላ ቃል የተናገርንበት ወይም ስግብግብነት የሚንጸባረቅበትን ፍላጎታችንን ለመሸፈን ብለን በማስመሰል የቀረብንበት ጊዜ እንደሌለ ታውቃላችሁ፤+ ለዚህም አምላክ ምሥክር ነው!  በተጨማሪም የክርስቶስ ሐዋርያት እንደመሆናችን መጠን እናንተን ብዙ ወጪ በማስወጣት ሸክም ልንሆንባችሁ እንችል የነበረ ቢሆንም እንኳ ከእናንተም ሆነ ከሌሎች ሰዎች ክብር ለማግኘት አልሞከርንም።+  ከዚህ ይልቅ የምታጠባ እናት ልጆቿን በፍቅር እንደምትንከባከብ እኛም በመካከላችሁ በነበርንበት ጊዜ በገርነት ተንከባከብናችሁ።  በመሆኑም ለእናንተ ጥልቅ ፍቅር ስላለን የአምላክን ምሥራች ለማካፈል ብቻ ሳይሆን ራሳችንን* ጭምር ለእናንተ ለመስጠት ቆርጠን ነበር፤+ ምክንያቱም እናንተ በእኛ ዘንድ እጅግ የተወደዳችሁ ነበራችሁ።+  ወንድሞች፣ ድካማችንንና ልፋታችንን እንደምታስታውሱ ጥርጥር የለውም። የአምላክን ምሥራች በሰበክንላችሁ ጊዜ፣ ማናችሁንም ብዙ ወጪ በማስወጣት ሸክም እንዳንሆንባችሁ+ በማሰብ ሌት ተቀን እንሠራ ነበር። 10  አማኞች ከሆናችሁት ከእናንተ ጋር በነበረን ግንኙነት ታማኞች፣ ጻድቃንና ነቀፋ የሌለብን ሆነን እንደተመላለስን ምሥክሮች ናችሁ፤ አምላክም ምሥክር ነው። 11  አባት+ ለልጆቹ እንደሚያደርገው ሁሉ እያንዳንዳችሁን እንዴት እንመክራችሁ፣ እናጽናናችሁና አጥብቀን እናሳስባችሁ+ እንደነበረ በሚገባ ታውቃላችሁ፤ 12  ይህን ያደረግነው ወደ መንግሥቱና+ ወደ ክብሩ+ በጠራችሁ አምላክ ፊት በአግባቡ መመላለሳችሁን እንድትቀጥሉ ነው።+ 13  በእርግጥም አምላክን ያለማቋረጥ የምናመሰግነው ለዚህ ነው፤+ ምክንያቱም የአምላክን ቃል ከእኛ በሰማችሁ ጊዜ እንደ ሰው ቃል ሳይሆን እንደ አምላክ ቃል አድርጋችሁ ተቀብላችሁታል፤ ደግሞም የአምላክ ቃል ነው፤ አማኞች በሆናችሁት በእናንተም ላይ በእርግጥ እየሠራ ነው። 14  ወንድሞች፣ ከክርስቶስ ኢየሱስ ጋር አንድነት ያላቸውን በይሁዳ የሚገኙትን የአምላክ ጉባኤዎች ምሳሌ ተከትላችኋል፤ ምክንያቱም እነሱ በአይሁዳውያን እጅ መከራ እየተቀበሉ እንዳሉ ሁሉ እናንተም በገዛ አገራችሁ ሰዎች እጅ ተመሳሳይ መከራ ተቀብላችኋል፤+ 15  አይሁዳውያን ጌታ ኢየሱስንና ነቢያትን ሳይቀር የገደሉ+ ከመሆኑም በላይ በእኛ ላይ ስደት አድርሰዋል።+ ከዚህም በተጨማሪ አምላክን እያስደሰቱ አይደለም፤ ከዚህ ይልቅ የሰውን ሁሉ ጥቅም የሚጻረሩ ናቸው፤ 16  አሕዛብ ይድኑ ዘንድ ለእነሱ እንዳንሰብክ ሊከለክሉን ይሞክራሉ።+ በዚህ መንገድ ሁልጊዜ ብዙ ኃጢአት ይፈጽማሉ። ይሁንና ቁጣው የሚገለጽበት ጊዜ ደርሷል።+ 17  እኛ ግን ወንድሞች፣ (በልብ ሳይሆን በአካል) ለአጭር ጊዜ ከእናንተ ለመለየት በተገደድንበት ወቅት እጅግ ስለናፈቅናችሁ ከእናንተ ጋር በአካል ለመገናኘት* ብርቱ ጥረት አደረግን። 18  በመሆኑም ወደ እናንተ መምጣት ፈልገን ነበር፤ አዎ፣ እኔ ጳውሎስ ከአንዴም ሁለቴ ሞክሬ ነበር፤ ሆኖም ሰይጣን መንገድ ዘጋብን። 19  ጌታችን ኢየሱስ በሚገኝበት ጊዜ በእሱ ፊት ተስፋችን ወይም ደስታችን ወይም የሐሴታችን አክሊል ምንድን ነው? እናንተ አይደላችሁም?+ 20  በእርግጥም እናንተ ክብራችንና ደስታችን ናችሁ።

የግርጌ ማስታወሻዎች

“ይሁንና በከፍተኛ ተጋድሎ” ማለትም ሊሆን ይችላል።
ወይም “ነፍሳችንን።”
ቃል በቃል “ፊታችሁን ለማየት።”